Thursday, October 24, 2013

መጽሐፈ ሲራክ

የሲራክ ልጅ የኢያሱ ጸሎት

 
አቤቱ ንጉስ ሆይ እገዛልሃለሁ፤ አቤቱ! አምላኬና መድኀኒቴ አመሰግንሃለሁ፤ በስምህም እታመናለሁ፤

ረድተኸኛልና ሰውረኸኝማልና፤ ሰውነቴንም ከሞት አድነኸዋልና፥ ከአንደበት የነገር ሥራ ወጥመድም አድነኸኛልና፥ ሐሰትንም     ከሚሰሩአት ከብዙ ሰዎች ምላስ አድነኸኛልና፥ በጠላትነትም ከተነሱብኝ ሰዎች ፊት የምትረዳኝና የምትሰውረኝ ሆነሃልና።

እንደ ቸርነትህ ብዛት መጠን ስለ ስምህ አዳንኸኝ። ይበሉ ዘንድ ያዘጋጁትን እንደሚያመሰኩ እንደዚሁ ባገኘችኝ በመከራዬ ብዛት   ሰውነቴን ፈለጓት።

ቋያ እንደ ከበበው፥ በእሳት መካከልም እንደማይቃጠል፥

ከታችም ከመቃብር ሆድ፥ ከረከሰ አንደበትም፥ ከሐሰት ቃልም አዳንኸኝ፤

ወደ ንጉስ በሚያጣላ ዐመፀኛ አንደበት፥ ሰውነቴ ወደ ሞት ደረሰች፤ ሕይወቴም ወደ መቃብር ደረሰች።

በዙሪያዬም ከበቡኝ፤ የሚረዳኝም አጣሁ፤ የሚያድነኝ ሰው እንዳለ ብዬ ተመለከትሁ፤ ግን ማንም አልነበረም።

አቤቱ ይቅርታህን ዐሰብሁ፥ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ የነበረ ሥራህን ዐሰብሁ አንተን ተስፋ የሚያደርጉ ሰዎች፥ ከጠላታቸውም የምታድናቸው ብፁዓን ናቸውና።

ልመናዬንም ከምድር ወደ ላይ ከፍ ከፍ አደረግሁ፤ ከሞት እድን ዘንድ ጸለይሁ።

አባቴና ጌታዬ እግዚአብሔርንም ረዳት በሌለበት፥ ትዕቢተኞች በተነሱበት ወራት በመከራዬ ጊዜ አትለየኝ አልሁት። 

፲፩ ስምህንም ለዘለዓም አመሰግናለሁ፤ እገዛልሃለሁ፤ ምስጋናህንም እናገራለሁ፤ ልመናዬን ሰማኸኝ።

፲፪ ከሞትም አዳንኸኝ፤ መከራ ከሚመጣበት ቀንም አዳንኸኝ፥ ስለዚህም ነገር እገዛልሃለሁ፥ አመሰግንሃለሁም። አቤቱ ስምህን አመሰግናለሁ።

፲፫ እኔ ሕፃን ሳለሁ ሳልሳሳት ጥበብን መረመርኋት፤ በጸሎቴም መረጥኋት።

፲፬ በቤተ መቅደስም ስለ እርስዋ ለመንሁ፤ ለዘለዓለምም እመረምራታለሁ።

፲፭ ፍሬዋም እንደ ተክል ፍሬ በዛ ልቦናዬም በእርስዋ ደስ አለው፤ እግሬም በእውነት ቆመች፤ ከሕፃንነቴም ጀምሮ ፍለጋዋን ተከተልሁ።

፲፮ በጆሮዬም ፈጽሜ አደመጥኋት፤ መረጥኋትም፤ እኔም ብዙ ጥበብን አገኘሁ።

፲፯ በእርሷም ከፍ ከፍ አልሁ፤ ጥበብን የሰጠኝን እግዚአብሔርን አመሰግነዋለሁ።

፲፰ አደርጋትም ዘንድ ዐሰብሁ፤ ለበጎ ነገርም ቀናሁ፤ አላፍርምም።

፲፱ ሰውነቴም በእርስዋ ተበረታታች፤ በሥራዬም ተራቀቅሁ፤ እጆቼንም ወደ ላይ አነሣሁ፤ ለድንቁርናዬም አለቀስሁላት።

ሰውነቴንም ወደ እርስዋ አቀናሁ፤ በንጽሕናም አገኘኋት፤ ልቡናዬንም ከመጀመሪያ ጀምሮ ከእርስዋ ጋር አጸናሁ፤ ስለዚህም እግዚአብሔር አልጣለኝም።

፳፩ ሰውነቴም ለእርስዋ ታወከች፤ መረመረቻትም፤ ስለዚህም መልካም ሀብትን ገንዘብ አደረግሁ።

፳፪ እግዚአብሔርም አንደበትን ዋጋ አድርጎ ሰጠኝ፤ በእርስዋም አመሰግነዋለሁ።

፳፫ እናንት አላዋቂዎች ወደ እኔ ቅረቡ፤ በጥበብ ቤትም ትኖራላችሁ።

፳፬ እንዴት አጣችኋት? እስኪ ንገሩኝ! ሰውነታችሁስ ፈጽማ እንደ ምን ተጠማች?

፳፭ አፌን ከፍቼ "ያለ ዋጋ ገንዘብ አድርጓት" ብዬ ተናገርሁ፤

፳፮ አንገታችሁን ዝቅ አድርጉ፤ ቀንበሯንም ተሸከሙ፤ ሰውነታችሁም ጥበብን ትቀበል፤ እርስዋን ማግኘት ቅርብ ነውና።

፳፯ እነሆ ጥቂት ደክሜ በእርስዋ ብዙ ዕረፍትን እንዳገኘሁ፤ በዐይናችሁ ተመልከቱ።

፳፰ ከብዙ ብር ይልቅ ጥበብን ምረጧት፤ ቊጥር ከሌለው ከወርቅ ይልቅ ገንዘብ አድርጓት።

፳፱ ሰውነታችሁም በቸርነቱ ደስ ይበላት፤ እርሱንም ማመስገን አትፈሩ።

በጊዜው ዋጋችሁን ይሰጣችሁ ዘንድ፤ ጊዜው ሳይደርስ ሥራችሁን ሥሩ። የሲራክ ጥበብ ተፈጸመ።